በሁለተኛው የሩብ ዓመት 6.27 ቢሊዮን ብር ትርፍ ከታክስ በፊት አግኝቷል

ላለፉት 128 ዓመታት የአገሪቱን የቴሌኮም አገልግሎት በብቸኝነት ሲያቀርብ የቆየው ኢትዮ ቴሌኮም፣ ከ62 ሚሊዮን ደንበኞቹ ሩብ ያህሉን የቴሌ ብር ተጠቃሚ ማድረጉን አስታወቀ፡፡

እስከተጠናቀቀው ሳምንት ድረስ ከ15.6 ሚሊዮን በላይ የሞባይል ገንዘብ ተጠቃሚ ደንበኞችን እንዳፈራ ያስታወቀው ኢትዮ ቴሌኮም፣ እነዚህ ደንበኞቹ በአገልግሎቱ ከ7.9 ቢሊዮን ብር በላይ ብር እንዲያዘዋውር ማስቻላቸውን ገልጿል፡፡

ከግንቦት 3 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ የሞባይል ገንዘብ ዝውውር ሲደረግበት በቆየው ቴሌ ብር ከታኅሳስ 10 ቀን 2014 ዓ.ም. ጀምሮ ይፋ በተደረገው ዓለም አቀፍ የሃዋላ አገልግሎት፣ ከ317 ሺሕ ዶላር በላይ የገንዘብ ዝውውር መከናወኑን የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሪት ፍሬሕይወት ታምሩ አስታውቀዋል፡፡

በዓለም አቀፍ የሞባይል ገንዘብ ሃዋላ ዝውውር ከሩብ ሚሊየን ዶላር በላይ እንደተንቀሳቀሰ የተገለጸ ሲሆን፣ ይህም ገንዘብ ከ25 የተለያዩ አገሮች ወደ አገር ቤት የተዘዋወረ መሆኑ ተመላክቷል፡፡

ሦስት ወራት ለመድፈን ጥቂት ቀናት በቀረው የቴሌ ብር ዓለም አቀፍ ሃዋላ አገልግሎት በርካታ የሃዋላ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር አብረው ለመሥራት ጥያቄ እንዳቀረቡ ያስታወቁት ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ፣ በዚህ ወቅት ኩባንያው ከአገልግሎት ሰጪ ተቋማቱ ጋር የውል ስምምነት ለማድረግ በሒደት ላይ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

እንደ ኩባንያው ገለጻ ካለፈው ግንቦት 2013 ዓ.ም. ጀምሮ 42 ሚሊዮን የሚደርስ የገንዘብ ዝውውር በቴሌ ብር የተፈጸመ ሲሆን፣ 67 ሺሕ የሚደርሱ ወኪሎች በዚህ ወቅት ከተቋሙ ጋር እየሠሩ እንደሚገኙ ተገልጿል፡፡

በአሁኑ ጊዜ 14 ሺሕ የሚደርሱ የንግድ ተቋማት አገልግሎታቸውን ከቴሌ ብር ጋር እንዳስተሳሰሩ ያስረዱት ወ/ሪት ፍሬሕይወት፣ 11 ባንኮች አገልግሎቱን ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር በጥምረት እየሰጡ እንደሚገኙ አስታውቀዋል፡፡

በሌላ በኩል ኢትዮ ቴሌኮም በሁለተኛው የሩብ ዓመት ከሚያቀርባቸው አጠቃላይ አገልግሎቶች 6.27 ቢሊዮን ብር ትርፍ ከታክስ በፊት እንዳገኘ ታውቋል፡፡

ኩባንያው በመጀመርያው የሩብ ዓመት ከታክስ በፊት ያገኘው ትርፍ 5.93 ቢሊዮን ብር እንደነበር የሚታወስ ሲሆን፣ ሆኖም ብልጫ ያለውን 6.27 ቢሊዮን ብር ያልተጣራ ትርፍ እንዳገኘ ተቋሙ የግማሽ ዓመቱን የዕቅድ አፈጻጸም ለመንግሥት የልማት ድርጅቶች ይዞታና አስተዳደር ባቀረበበት መድረክ ላይ ሪፖርት ተደርጓል፡፡

ኢትዮ ቴሌኮም በግማሽ ዓመቱ አገኘዋለሁ ብሎ ካቀደው 32 ቢሊዮን ብር ገቢ ውስጥ 28 ቢሊዮን ብር የሚደርስ ገቢ ማስመዝገቡን፣ ከግብር በፊት ለማግኘት ካቀደው 12.4 ቢሊዮን ብር ትርፍ ደግሞ 12.2 ቢሊዮን ብር ያህል ማኘቱ ተገልጿል፡፡

በመጀመርያው ሩብ ዓመት ኩባንያው ከግብር በፊት 4.88 ቢሊዮን ብር ትርፍ ለማግኘት አቅዶ 5.93 ቢሊዮን ብር ትርፍ እንዳገኘ የሚታወስ ሲሆን፣ ይህ አኃዝ የ6.27 ቢሊዮን ብር ትርፍ ታክሎበት በግማሽ ዓመቱ በአጠቃላይ 12.2 ቢሊዮን ብር ውጤት እንዲዘገብ አስችሏል፡፡

ኢትዮ ቴሌኮም ከአጠቃላይ ገቢ አንፃር በግማሽ ዓመቱ ይገኛል ተብሎ ከጠበቀው 32 ቢሊዮን ብር በአራት ቢሊዮን ብር ያነሰ የ28 ቢሊዮን ብር ገቢ እንዳገኘ የሚታወስ ሲሆን፣ ሆኖም በሁለተኛው ሩብ ዓመት የተመዘገበው 14.46 ቢሊዮን ብር ገቢ በመጀመርያው ሩብ ዓመት ተመዘግቦ ከነበረው የ13.54 ቢሊዮን ብር ብልጫ የታየበት አንደነበር በግምገማ ወቅት የቀረበው አኃዝ ያሳያል፡፡

ይህ በዚህ እንዳለ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትራፊክ ማኔጅመንት ኤጀንሲ፣ የትራፊክ ደንብ ተላላፊ አሽከርካሪዎች የቅጣት ክፍያ ሥርዓትን የሚያቀላጥፍና  የሚያዘምን አዲስ አሠራርን ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር ይፋ አድርጓል፡፡

የትራፊክ ደንብ ቅጣት ክፍያን በቴሌ ብር አማካይነት መክፈል የሚያስችለው ይህ አገልግሎት ለዘመናት አድካሚ የነበረውን በወረቀት ላይ ያተኮረ የቅጣት ክፍያ አፈጻጸም፣ የሚያስቀር ሲሆን፣ በተለይ አሽከርካሪዎች የቅጣት ክፍያውን ለመፈጸም የሚወስድባቸውን ጊዜ በመቆጠብና ድካምን የሚያስቀር ዘመናዊ አገልግሎት ከመሆኑም ባሻገር፣ መንግሥት ለመቅጫ ፓድ ኅትመት የሚያወጣውን ወጪንም ያስቀራል ተብሏል፡፡

Leave a Reply

Required fields are marked *